Thursday 6 March 2014

(ሰበር ዜና) መርዝ ተሰጥቷቸዋል የተባሉት የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ኦቦ ዓለማየሁ አቶምሳ አረፉ

ለህክምና ብዙ ገንዘብ ወጣባቸው በሚል ሕገወጥ በሆነ መንገድ ከስልጣናቸው እርሳቸው ባላወቁበት በፈቃዳቸው እንደለቀቁ ተደርጎ የተነገረባቸው የኦሮሚያው ክልል ፕረዚዳንት ኦቦ አለማየሁ አቶምሳ በተሰጣቸው የተመረዘ ምግብ ምክንያት የጀመራቸው በሽታ በከፍተኛ ሁኔታ ጸንቶ በተደጋጋሚ በተለያዩ ሃገራት ህክምናቸውን ሲከታተሉ የቆዩ ሲሆን ዛሬ ግን በባንኮክ ታይላድ ለህክምና በሄዱበት ሆስፒታል ሕይወታቸው አልፏል።
በ45 ዓመታቸው በታይላንድ ባንኮክ ሕይወታቸው ያለፈው ኦቦ ዓለማየሁ አቶምሳ በምን ምክንያት የተመረዘ ምግብ እንደተሰጣቸው ባይታወቅም ከርሳቸው ጋር ምግቡን በልቶ የነበረ ግለሰብም እስካሁን በሞት አፋፍ ላይ እንደሚገኝ ለዘ-ሐበሻ የደረሱ መረጃዎች ያመለክታሉ። ለዘ-ሐበሻ ቅርብ የሆኑ የኦነግ የመረጃ ምንጮች “ኦህዴድን የድሮው ኦህዴድ እንዳይሆን ሊያደርጉ የሚችሉ ሰው ስላልነበሩ በሕወሓቶች መርዝ እንዲሰጣቸው ተደርጓል” የሚል አመለካከት ያላቸው መሆኑን ገልጸው ሕወሓት አቶ ዓለማየሁን ቀጠፋቸው ሲሉ ይተቻሉ”፡
ከየካቲት ወር መጀመሪያ ጀምሮ በባንኮክ ህክምና ላይ የከረሙት በምስራቅ ወለጋ ቢሎ ቦሼ ወረዳ ከአባታቸው አቶ አቶምሳ ሚጃ እና ከእናታቸው ወይዘሮ አየለች ብሩ በ1961 ዓ.ም ተወለዱት አቶ ዓለማየሁ አቶምሳ ሕይወታቸው በእንዲህ ያለ ሴራ ማረፉ በኢሕአዴጎች መካከል አለመተማመንን ሊፈጥር እንደሚችል የተለያዩ የፖለቲካ ታዛቢዎች እየገለጹ ነው።


የኦህዴድ/ኢህአዴግ ማዕከላዊ ኮሚቴ ፅህፈት ቤት ዛሬ ባወጣው መግለጫ አቶ ዓለማየሁን “ላለፉት 24 ዓመታት የኦሮሞ ህዝብ እና መላው የአገሪቱ ህዝቦች ዛሬ ለደረሱበት የሰላም፣ የዴሞክራሲና የልማት ተጠቃሚነት እንዲበቁ በቁርጠኝነት የታገሉ ነባር ታጋይ ነበሩ” ካለ በኋላ በ1981 ዓመተ ምህረት የደርግን ስርዓት ለመገርሰስ ሲካሄድ የነበረውን የትጥቅ ትግል መቀላቀላቸውን፣ ከ1988 እስከ 1994 ድረስም የኦህዴድ ማዕከላዊ ፅህፈት ቤት እና የድርጅቱ የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ በመሆን ማገልገላቸውን፣ ከ2002 ዓመተ ምህረት ጀምሮ የኦህዴድ ሊቀመንበር ሆነ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር መሆናቸውን ጠቅሷል። ሆኖም ግን ድርጅቱ እንደተጠበቀው አቶ አለማየሁ በተመረዘ ምግብ መሞታቸውን ከሴራው በስተጀርባ ማን እንዳለ ያስቀመጠው ነገር አለመኖሩን የዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች ጠቁመዋል።
በሌላ በኩል ለዘ-ሐበሻ በደረሱ መረጃዎች ቀጣዩ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ወ/ሮ አስቴር ማሞ ይሆናሉ የሚለው ግምት ሚዛን እየደፋ ነው።

No comments:

Post a Comment